lørdag 27. juli 2013

“ ከሙስና”ው ክስ በስተጀርባ (ተመስገን ደሳለኝ)


የኢትዮጵያ ፖለቲካ ለትንተና አዳጋች መሆኑን የሚናገሩ ምሁራን መከራከሪያቸው ፖለቲከኞቹ ከርዕዮተ-ዓለም ይልቅ ‹‹ሴራ››ን
ማስቀደማቸውን በመጥቀስ ነው፡፡ በርግጥም አብዛኛው የፓርቲዎቹ የአመራር አባላት ከክህሎት እና ርዕዮተ-ዓለም መራቀቅ ይልቅ
በዘልማዱ ፖሊቲካ የተካኑ ናቸው፡፡ በተለይም የ1966ቱ ‹‹አብዮት›› ያሰረፀው የ‹‹ፓርቲ ፖለቲካ›› የተደራጀ ‹‹ሴራ›› ምን ያህል
ኩነትንም ታሪክንም መቀየር እንደሚችል አሳይቷል፡፡
የሁሉንም ፓርቲ የአመራር አባላት አመዳደብ መስፈርት ከምር ከፈተሽነው ከፊት መስመር ከምናገኛቸው አብዛኞቹ በዚህ አይነቱ
የጨዋታ ህግ የተሻሉ ሆነው ስለተገኙ መሆኑን ለመረዳት አያዳግትም (ሻዕቢያ፣ ኦነግ፣ ደርግ፣ ኢህአፓ-እነጌታቸው ማሩንና
ብርሃነመስቀል ረዳን፣ ህወሓት-እነስሁል፣ እነአረጋዊ፣ እነስዬ፣ ብአዴን-እነያሬድ ጥበቡንና ሙሉዓለም አበበን፣ ኢህአዴግ፣ መኢአድ፣
ኢዴፓ፣ ቅንጅት፣ አንድነት… የመርህና የህግ ተገዥ የሆኑ አመራሮቻቸውን ደግመው ደጋግመው በሴራ ፖለቲካ በጓሮ በር ሸኝተዋል)
የዚህ ፅሁፍ ዓላማ አውራው ኢህአዴግ፣ በተለይም ከድህረ ትጥቅ ትግሉ ወዲህ ባለተፃፈ ህጉ በመሪዎቹ ላይ የፈፀማቸውን የሴራ
ፖለቲካ ለመቃኘት መሞከር ነው፡፡ እንደ ሚታወቀው ስርዓቱ ወደስልጣን ከመጣ በኋላ ተአማኒነትን ያላገኙ ግዙፍ የፖለቲካ
እርምጃዎችን በጉምቱ መሪዎቹ ላይ በተደጋጋሚ ሲወስድ አይተናል (በተጠመደ ፈንጅ ህይወቱ ያለፈውን የብአዴን መሪ ሙሉዓለም
አበበንና የጄኔራል ሀየሎም ግድያን ሳንጨምር)
ታምራት ላይኔ
ኢህአዴግ እንደመንግስት ከተሰየመ በኋላ ‹‹በህገወጥ ብልፅግና›› ስም የመጀመሪያው ትልቁ ሰለባ ያደረገው ምክትል ጠቅላይ ሚንስትር
ታምራት ላይኔን ነበር፡፡ በወቅቱ የታምራት መከሰስ ታምራት በትግሉም ሆነ በመንግስትነት ዘመኑ ከነበረው ከፍተኛ ኃላፊነት አኳያ
እና በአንደበቱ ‹‹ተመክሬ፣ ተዘክሬ አልሰማ ብያለሁ›› ከማለቱ አንፃር ግንባሩ ሙስናን ለመዋጋት ቁርጠኝነት ያለው አስመስሎት ነበር፡፡

ነገር ግን ምክትል ጠቅላይ ሚንስትሩ ዘርፏል ከተባለው በእጅጉ የሚልቅ መጠን ያለው የሀገር ሀብት ‹‹ሌባ›› ብለው ያሰሩት ጓደኞቹ
ሲዘርፉ መመልከታችን፣ እንዲሁም ታምራት ከታሰረ በኋላ በድርጅታዊ ግምገማ ወቅት ሲጠየቁ ‹‹ዘርፌያለሁ›› ብለው ግለ-ሂስ ያወረዱ
የኦህዴድ ባለስልጣናት ፍርድ ቤት ሲቀርቡ አለማየታችን ‹‹ወርቁ››ን ከ‹‹ሰሙ›› ለመለየት ብዙ እንዳንጠብቅ አድርጎናል፡፡ ይህ ግን
ታምራት ህገ-ወጥ ብልፅግና ውስጥ እጁን አልከተተም ማለት አይደለም፡፡ የዚህ ፅሁፍ ማዕከላዊ ሃሳብም የየትኛውንም የኢህአዴግ
ባለሥልጣናትን ‹‹ንፅህና›› መስበክ አይደለም፡፡ ፍላጎቴ ለኢህአዴግ ‹‹አላግባብ ብልፅግና›› ተቀናቃኝን መምቻ ነውን? ወይስ የሀገር ሃብት
ዘረፋን ለመከላከል ቆርጦ ስለተነሳ ነው? በሚሉት ጥያቄዎች ላይ የግል ምልከታን ማስቀመጥ ነው፡፡
ስዬ አብርሃ
ስርዓቱ የሙስና ሰለባ ያደረገው ሌላኛው ባለስልጣን ስዬ አብርሃ (ለታምራት ላይኔ ሳይቀር ወታደራዊ ስልጠና የሰጠው) እንደሆነ
ይታወቃል፡፡ እዚህም ጋ ስዬን ‹‹ጲላጦስ›› የማድረግ ፍላጎት የለኝም፤ ነገር ግን ስዬ በ‹‹ሙስና›› ተወንጅሎ ለአመታት እስር ቤት
የተወረወረው ከቀድሞ ጠቅላይ ሚንስትር ጋር በኤርትራና በመሰል አንዳንድ ጉዳዮች ላይ መለያየታቸውን (አለመስማማታቸውን)
ተከትሎ መሆኑ ጉዳዩ ‹‹ሙስና› ብቻ እንዳልሆነ ያመላክታል፡፡ ምክንያቱም በወቅቱ የሃሳብ ልዩነቱ ከመለስ ጋር አኳርፏቸው ከድርጅቱ
የታገዱት ከፍተኛ የአመራር አባላት ከሰባት በላይ ሲሆኑ፣ የታሰረው ግን ስዬና ቤተሰቦቹ ብቻ ነበሩ፡፡ ይህ ሁኔታም ‹‹ስዬ ከሰራዊቱ ጋር
ያለው ቁርኝት ለመለስ ስልጣን አስጊ ስለሆነ ነው ከአቻዎቹ ተነጥሎ ለእስር የተዳረገው›› ወደሚል ጠርዝ የገፉኝን ጥቂት ምክንያቶች
እጠቅሳለሁ፡፡
 ፩
ስዬ በህገወጥ-ብልፅግና ላይ መሳተፉ ከተረጋገጠ፣ በህግ ለመጠየቅ የግድ ህወሓት ለሁለት ተከፍሎ፣ ስዬም የመንግስት ስልጣን ከያዘው
ኃይል በተቃራኒው እስኪሰለፍና ከድርጅቱ እስኪባረር መጠበቁ አንዱ ነው፡፡ እህትና ወንድሞቹም በተመሳሳይ መንገድ ለእስር
መዳረጋቸው ጉዳዩን ህግ ከማስከበር ይልቅ ወደበቀል ያመዘነ አስመስሎታል (በነገራችን ላይ ከነመላኩ ፈንታ ጋር የታሰረው ምረህትአብ
አብርሃ የስዬ ታናሽ ወንድም ሲሆን፣ በ93ም ከስዬ ጋር አብሮ ለወራት ታስሯል)

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar