onsdag 6. februar 2013

የጎልጉል ቅምሻ/(ከዚህም ከዚያም)


 ሐላል ምግብ ውስጥ የአሳማ፤ በርገር ሥጋ ውስጥ ደግሞ የፈረስ ዲኤንኤ ተገኘ
በእንግሊዝ አገር ለእስረኞች ሐላል ምግቦችን የሚያቀርቡ ድርጅቶች (ቸርቻሪዎች) በሚያቀርቡት ሥጋም ሆነ የጣፋጭ ምግብ ውጤቶች ውስጥ የአሳማ ሥጋ (ዲኤንኤ) እንደሚገኝ ከታወቀ ወዲህ በርካታዎቹ ለእስርቤቶቹ ምግብ ማቅረባቸውን እንዲቋረጥ የፍትህ ሚ/ር አዝዟል፡፡
በበርካታ አገራት የፈጣን ምግብ አቅራቢ እንደሆነ የሚታወቅ በርገር ኪንግ በሚሸጠው የበርገር ሥጋ ውስጥ የፈረስ ዲኤንኤ እንደሚገኝ ባለፈው ሐሙስ አምኗል፡፡ የአሳማ ሥጋ መገኘቱ ከታወቀ ወዲህ በርካታ ሙስሊም እስረኞች ተቃውሟቸውን እየገለጹ ሲሆን የፍትህ ሚ/ር በአቅራቢዎቹ ላይ እርምጃ እንደሚወሰድ ቃል ሰጥቷል፡፡ በጉዳዩ ላይ ከፍተኛ ሐዘን የተሰማቸው ሙስሊም አስተያየት ሰጪዎች ጉዳዩ ሆን ተብሎ የተደረገ ጉዳይ በመሆኑ ሙስሊሙ ኅብረተሰብ በሙሉ በአንድ ድምጽ መነሳት እንዳለበት አሳስበዋል፡፡

$120ቢሊዮን ዶላር ወዳገርቤት

በቅርቡ በተጠናቀቀው የአውሮጳውያኑ ዓመት (2012) በአሜሪካ የሚገኙ ስደተኞች ወደየአገሮቻቸው የላኩት ገንዘብ ከ120 ቢሊዮን ዶላር በላይ እንደነበር ተገለጸ፡፡ ከዚህ ውስጥ ከ23ቢሊዮን ዶላር በላይ የሚሆነው ወደ ሜክሲኮ፣ ከ13ቢሊዮን ዶላር በላይ ወደ ቻይና፣ 11ቢሊዮን ዶላር አካባቢ የሚሆነው ወደ ሕንድ፣ 10ቢሊዮን ወደ ፊሊፒንስ በመላክ ቀዳሚ አገራት ሆነዋል፡፡
በዚህ ጉዳይ ላይ ስኬት በማስመዝገብ ከቀዳሚ አገራቱ መካከል ለመሆን ያልቻለው ኢትዮጵያን የሚገዛው ኢህአዴግ ጉዳዩን በቸልታ ማለፍ እንደማይገባው ደጋፊዎቹና የጥቅም ተካፋዮቹ በጥብቅ የሚያነሱት ጉዳይ ነው፡፡ በሕዳሴውም ሆነ በአምስት ዓመቱ ታላላቅ የረጅም ጊዜ ዕቅዶችም ይሁን በሌሎች ጥቃቅንና አነስተኛ ዕቅዶች በጉዳዩ ላይ በጥብቅ መክሮበትና ያወጣቸውን ህጎች በመጠቀም የኤክስፖርት ንግዱን በማጧጧፍ ገቢ የሚጨምርበትን መንገድ ሊቀይስ እንደሚገባው ያሳስባሉ፡፡

“እጃችሁን ታጠቡ!” ለህጻናት ብቻ ሳይሆን ለወንዶችም ጭምር

ከዚህ ቀደም የተካሄዱ ጥናቶች እንደሚጠቁሙት የሕዝብ መጸዳጃዎችን ከተጠቀሙ በኋላ ከ90 በመቶ በላይ ሴቶች እጃቸውንየሚታጠቡ ሲሆን የወንዶች ቁጥር ግን 75በመቶ አካባቢ እንደሆነ ይመሰክራሉ፡፡
ሰሞኑን በኮሌጆችና በርካታ ወንዶች በሚጠቀሙባቸው የሕዝብ መጸዳጃዎች አካባቢ የተከናወነ ጥናት እንደጠቆመው እጅ መታጠብ አስፈላጊ መሆኑን የሚጠቁም ማስታወቂያና ማሳሰቢያ በመጸዳጃ ቤቶች ከተለጠፈ በኋላ እጃቸውን የሚታጠቡ ወንዶች ቁጥር በእጅጉ መጨመሩን ያስረዳል፡፡ በመሆኑም አዋቂ ወንዶች እንደ ህጻናት እጃቸውን መታጠብ እንዳለባቸው ሊነገራቸው ይገባል ወደሚል መደምደሚያ ደርሷል፡፡

በክርስቲያን ት/ቤት ህጻናት በወሲብ ተጠምደዋል

በካሊፎርኒያ ጠቅላይግዛት በሚገኝ የሉተራን መዋዕለህጻናት ውስጥ የሚገኙ የ4፣ 5 እና 6ዓመት ህጻናት እርስበርሳቸው በአፍ ወሲብ ድርጊት ተጠምደው እንደሚውሉ ይፋ ሆኗል፡፡
ጸያፍ ድርጊቱ የሚፈጸመው በዕረፍትና መኝታ ጊዜያቸው እንደሚሆን የተነገረ ሲሆን በድርጊቱ የተቆጡ ወላጆች ድምጻቸውን ካሰሙ በኋላ ት/ቤቱ ትምህርት መስጠቱን አቋርጧል፡፡ በሃይማኖት ድርጅቶች ልጆቻቸውን እንዲማሩ የሚልኩ ወላጆች ኃላፊነቱን ሙሉ በሙሉ በት/ቤቱ ላይ ከማሳረፍ ይልቅ የራሳቸውን ልዩ ቁጥጥር ማድረግ እንደሚገባቸው የሚናገሩ በርካታዎች ይናገራሉ፡፡ ሌሎች ግን ህጻናቱን እንደዚህ ዓይነት ጸያፍ ድርጊት እንዲፈጽሙ ማን ሊያሳያቸው ቻለ፤ ማንስ አስተማራቸው በማለት ምላሽ የሚሻ ጥያቄ ያቀርባሉ፡፡ በዓለማችን ክፋትና ርኩሰት እየበዛ በመሄዱ ወላጆች ለራሳቸውም ሆነ ለልጆቻቸው ሃይማኖትንና ግብረገብነትን በትጋት ሊያስተምሩ ይገባል በማለትም ይመክራሉ፡፡

የጂፒኤስ መዘዝ

ወጣቶቹ የጓደኛቸውን ቤት ለማግኘት በጂፒኤስ እገዛ ጉዟቸውን አቅንተዋል፡፡ መንገድ ጠቋሚው መሣሪያም እነሆ ካሰባችሁበት ደርሳችኋል ሲላቸው ከደረሱበት ቤት የጠበቃቸው ግን ጓደኛቸው አልነበረም፡፡
በጆርጂያ ጠቅላይ ግዛት ነዋሪ የሆነውና የቪየትናም ጦርነት አርበኛ የ69ዓመቱ አዛውንት ግን ወደ ቤቱ የመጡት ወጣቶች ዘራፊዎች እንደሆኑ በመቁጠር ገና ከመኪና ሳይወርዱ ቪየትናምን አስታወሰባቸው፡፡ በተኩሱ የመኪናዋ አሽከርካሪ የ22 ዓመቱ ወጣት ሲገደል መኪናው ውስጥ የነበሩት ሁለት ወጣቶች ሁኔታውን ለፖሊስ አስረድተዋል፡፡ አዛውንቱ ያለዋስ በማረፊያ ቤት ሆኖ ፍርዱን እየተጠባበቀ ነው፡፡

ዕዳ በልጅ ሲከፈል

በቅርቡ በወጣ ዶክሜንታሪ ፊልም በአፍጋኒስታን የሚገኙ ገበሬዎች ብድራቸውን ለመክፈል ሲያቅታቸው የአደንዛዥ ዕጽ አዘዋዋሪ ጌቶቻቸው ልጆቻቸውን እንደክፍያ እንደሚወስዱባቸው ዘግቧል፡፡ ገበሬዎቹ ለዕዳቸው የሚከፍሉትን ሲያጡ ያሏቸውን ወንድም ሆነ ሴት ልጆቻቸውን እንዲሰጡ የሚገደዱ ሲሆን አስገባሪዎቻቸውም ልጆቹን (አንዳንዶቹ የ10ዓመት ህጻናት የሆኑ) ወደ ፓኪስታንና ኢራን ለወሲብ ባርነት እንደሚሸጧቸው ፊልሙ ጨምሮ ዘግቧል፡፡ ሴት ልጁን አልሰጥም ያለ አንድ አባት ለሌላው መቀጣጫ እንዲሆን አንገቱ ተቀንጥሷል፡፡
እስልምና ሃይማኖት ጥብቅ በሆነባት አፍጋኒስታን እንደዚህ ዓይነቱ አሰራር ሃይማኖቱን የሚያጎድፍ እንደሆነ አስተያየት ቢሰጥም ሌሎች ግን የሃይማኖቱ ጽንፈኝነት ያመጣው ጣጣ ነው በማለት ይኮንናሉ፡፡

ፕሬዚዳንታዊ ትጋት

በለውጥ መዓበል የምትታመሰው ሶሪያ ፕሬዚዳንት ባሽር አልአሳድ በመጪው መጋቢት ወር ልጅ ያገኛሉ ተብሎ እየተጠበቀ ነው፡፡ ወሬውን ሙሉ በሙሉ ለማረጋገጥ ባይቻልም ታማኝ ምንጮቻቸውን ጠቅሰው በመካከለኛው ምስራቅ የሚገኙ የዜና ወኪሎች የወሬውን እውነተኛነት እያረጋገጡ ይገኛል፡፡
ሶሪያ ያለችበትን ሁኔታ የሚከታተሉና ዜናው ያስገረማቸው አስተያየት ሰጪዎች በዚህ ሁሉ ደም መፋሰስ ውስጥ ፕሬዚዳንቱ በልጅ መውለድ (ማስወለድ) በኩል ያሳዩትን “ትጋት” በማድነቅ አላግጠዋል፡፡
የሳምንቱ ምርጥ ፎቶ
ሰሞኑን የፈረንሳይ ፓርላማ የግብረሰዶማውያንን ጋብቻ ለማጽደቅ በመከረበት ጊዜ ፕሬዚዳንቱ ፍራንሷ ኦላንድ የሚመሩት የሶሻሊስት ፓርቲ አባላት በሌላ ጉዳይ ላይ ተጠምደው ነበር፡፡ ሁለቱ የሶሻሊስት ፓርቲ የፓርላማ አባላት iPad ላይ ቃላትን የመደርደር ጨዋታ በመጫወት ሲፎካከሩ ታይተዋል፡፡
እነዚህ ሁለት የሕዝብ እንደራሴዎች ወደ ኢትዮጵያ ተልከው በአንድ የተቃዋሚ ፓርቲ አባል የታጀበውና 547 መቀመጫ ካለው ትጉህ የኢህአዴግ ፓርላማ አባላት ልምድ ይቀስሙ ዘንድ በቅጣት መልክ ወደዚያ እንዲላኩ እዚያው በአምባሳደርነት የሚገኙት የቀድሞው አፈጉባዔ ተሾመ ቶጋ የማያሳስቡ ከሆነ የዕድገትና ትራንስፎርሜሽኑ ዕቅድ በፈረንሳይ ከሽፏል የሚያሰኝ ነው፡፡
ዘገባውን ለማጠናቀር በየጽሁፉ ከጠቀስናቸው ምንጮች በተጨማሪ ሌሎችንም የሚዲያ ውጤቶች መጠቀማችንን ለመግለፅ እንወዳለን፡፡ ከዜናዎቹ ማነስ አኳያ በየጸሁፉ ለመግለጽ ባለመቻላችን ይቅርታ እንጠይቃለን፡፡

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar