fredag 15. august 2014

ብሄርተኝነትን ታጥቀው አገራችንን ወደ አደገኛ ጠርዝ ከሚገፏት ምሁራን መካከል፣ የተወሰኑት ላይ የአቅሜን ያህል ሂስ ለመሰንዘር

የፕሮፌሰር ጌታቸው ነገር!
ወርቁ ፈረደ

ሞክሬያለሁ፡፡ አሁን ደግሞ የፕሮፌሰር ጌታቸውን አንዳንድ የተዛቡ ሀሳቦች ለመዳሰስ እሞክራለሁ፡፡

ፕሮፌሰር ጌታቸው አንቱ የሚባሉ ምሁርና አንተ የሚባሉ ፖለቲከኛ ናቸው፡፡ ጥናቶቻቸውን አንብቦ በእውቀታቸው ስፋት እና በጽሁፍ
ችሎታቸው የማይደነቅ ሰው ማግኘት ይከብዳል፡፡ ያም ሆኖ ጌቾ በመጣጥፎቻቸው፣ በግለ ታሪካቸው፣ እንዲሁም የአባ ባህርይ
ድርሰቶችን በሰበሰቡበትና ባሰናዱበት ጥራዛቸው የሚያንጸባርቋቸው አንዳንድ የተዛቡና አደገኛ ሐሳቦች አብረው የሚያኗኑሩ አይደሉም:፡

ለምሳሌ በቅርቡ፣ በአንዳንድ የኦሮሞ ብሄርተኞች በኩል ለሚሰነዘሩ ዘለፋዎች ምላሽ እንዲሆን የጻፉትን “ዕርቅና ሰላም፣ የሕይወት
ቅመም” የተባለ መጣጥፋቸውን ያነበበ ሰው፤ አንጋፋ ምሁራኖቻችን ከዕርቅና ከሰላም ጋራ እንዴት አድርገው እንዳቆራረጡን መረዳት
አያቅተውም፡፡

ጌቾ፣ ለአገሪቱ ቅርስ ውድመት የእስልምና እምነትና የኦሮምኛ ተናጋሪ ጎሳዎችን ተጠያቂ አድርገዋል፡፡ እርግጥ ነው፣ የግራኝ አህመድ ጦር
ወደ መሀል አገር በዘመተ ጊዜ እንዲሁም የኦሮሞ ገዳ ጦር አንዳንድ የአገሪቱን ክፍሎች በጦር ባስገበረ ጊዜ አያሌ ሰብአዊ፣ ቁሳዊና
መንፈሳዊ ሀብቶች ላይ ውድመት መድረሱ የተረጋገጠ ነው፡፡

ይሁን እንጂ አውዳሚነትን ከአንድ ብሄረሰብ እና ከአንድ ሀይማኖት ጋር አያይዞ ማቅረብ አድልኦ እንጂ እውቀት ሊሆን አይችልም፡፡
ዋናው የውድመት ምንጭ ሁሉም ብሄረሰቦችና ሁሉም ሀይማኖቶች የሚጋሩት የጦርነት ባህላችን ነው፡፡ በጦርነት ወቅት ክርስትያን
ነገስታትም ቤተ-ክርስትያን አቃጥለዋል፡፡ ቅርስ በዝብዘዋል፡፡ ለምሳሌ፣ አለቃ ወልደማርያም በጻፉት ዜናመዋእል ውስጥ በጎንደር
ስለተካሄደ አንድ ጦርነት ሲዘግቡ “(ቴዎድሮስ) በጎንደር ቤተክርስትያን በከተማው ውስጥ ያለውን አቃጠሉ፡፡ ከከተማው የራቀው ግን
በእግዜር ትእዛዝ ተረፈ” ይላሉ፡፡

ቴዎድሮስ እና አብዛኞቹ ወታደሮቻቸው የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች ነበሩ፡፡ ነገር ግን ኦርቶዶክስነታቸው፣ ከሙስሊሙ ወይም
ከአገር-በቀል እምነት ተከታዩ የተሻለ ለቅርስ እንዲራሩ አላደረጋቸውም፡፡ ስለዚህ አንዱን እምነት በቅርስ ፈጣሪነት፣ ሌላውን በቅርስ
አውዳሚነት መፈረጅ ኢ-ታሪካዊ ይመስለኛል፡፡

ፕሮፌሰሩ በብሄረሰቦች ጥናት ላይ ያላቸውን እውቀት ለማዋጣት ደክመዋል፡፡ ይሁን እንጂ እውቀታቸው በፍርዳቸው ሲበላሽ እናያለን፡፡
የትግራይ ብሄር ተወላጆችን ሳያስቆጡ ስለ ትግራይ፣ የኦሮሞ ተወላጆችን ሳያስቆጡ ስለ ኦሮሞ መናገር ያቅታቸዋል፡፡ ለምሳሌ በአባ
ባህርይ መጽሐፋቸው፣ ኦሮሞ የሚለውን መጠርያ በነውረኝነት ከሚጠቀሰው መጠርያ በኋላ የመጣ አስመስለው ለማሳመን ሞክረዋል፡፡
ያ ቃል ከጥንት የኖረ ለመሆኑ ጥንታውያን ጸሐፊዎቹን እነ አባ ባህርይን፣ አለቃ አጥሜንና አለቃ ታዬን በዋቢነት ይጠቅሳሉ፡፡

ምክንያታቸው ምንም ይሁን የተጠቀሱት ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት በኦሮሞ ጥናት ላይ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን
መጽሀፋቸውን ያነበበ ሁሉ የሚረዳው ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከአድልኦ የነጹ አልነበሩም፡፡ የሚበይኑት ብያኔ፣ የሚጠቀሙት ስያሜ ሁሉ
በባእድ አስተያየት የተቃኘ ነው፡፡ በሌላ በኩል፣ በዘመነ መሳፍንት ማክተሚያ ላይ በኦሮሞ መካከል ኖሮ፣ የመስክ ጥናት ያካሄደው
አንቶኒዮ ደ አባዲ ኦሮሞዎች ራሳቸውን ኦሮሞ ብለው እንደሚጠሩ ጽፏል፡፡ “የኢትዮጵያ ጂኦግራፊ” በተባለው ስራው ውስጥ ቃሉን ቸል
ብሎ ኦሮሞ የሚለውን ቃል ይጠቀማል፡፡ እንዲሁም የአለቃ አጥሜና የአለቃ ታዬ ዘመነኛ የሆነው ቦረሊ በመጽሐፉ ኦሮሞ የሚለውን
ቃል ሲገለገልበት እናያለን፡፡ ይህ የሚያሳየው ቃሉ ዘመን አመጣሽ ሳይሆን የብሄረሰቡ ቤተሰባዊ መጠርያ ሆኖ ከጥንት የነበረ መሆኑን
ነው፡፡

ጌቾ፣ ስለ ጥንታዊው የኦሮሞ ወታደር የጦር ዘይቤ ሲጽፉ ያቀረቡት ፍርድ ከርሳቸው የሚጠበቅ ሆኖ አላገኘሁትም፡፡ እንዲህ ይላሉ፤
“ድንገት ካልተደረሰባቸው በቀር ምንም ቢሆን ከጠላት ጦር ጋራ ፊት ለፊት ውጊያ አይገጥሙም፡፡ የጦር ሀይል መምጣቱን ሲሰሙ
በተገኘው አቅጣጫ ሁሉ ይሸሻሉ፡፡ ሲሸሹ ገደል አይመልሳቸውም”

ይህን ፍርድ፣ በጌቾ አእምሮ ውስጥ እንጂ በእውነተኛው ታሪክ ውስጥ አናገኘውም፡፡ የአባ ባህርይ ዘመነኛ የሆኑት የኦሮሞ ተዋጊዎች
ስመ-ጥር ጀግኖችና ድል ነሺዎች እንደነበሩ ከጠላት ወገን የሆኑ መንገደኞች ሳይቀር መስክረውላቸዋል፡፡ ለምሳሌ፣ ፓንክረስት
በገላውድዮስና በኦሮሞ አስገባሪዎች መካከል የተደረጉ ጦርነቶችን በማስመልከት ቤርድሙዝን ጠቅሶ ሲጽፍ ይህን ይላል
“ስለ ኦሮሞዎች ችሎታና በንጉስ ገላውዲዎስ ላይ የተቀዳጁትን ድል አስመልክቶ ቤርድሙዝ ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡ ከአንድ ውጊያ በኋላ
ንጉሱ የረባ ነገር ሳይፈጽም፣ ተረትቶና ደካክሞ ወደ ሰፈሩ ተመለሰ፡፡ ከጥቂት አለፍ ብሎ ቤርድሙዝ፣ ንጉሱ በኦሮሞዎች ተሸንፎ
በውርደት ለመሸሽ መገደዱን መዝግቧል›› (The Ethiopian borderlands. ገፅ 284)

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar