fredag 15. mars 2013

ፕሮፌሰር መስፍን የድብትርናን ሹመት የሚሰጡ በሆኑና በተቀበልኳቸው ደስታውን አልችለውም” ዲ/ን ዳንኤል ክብረት


(አንድ አድርገን መጋቢት 5 2005 ዓ.ም)፡- በዚህ ሰሞን የብዙዎች መነጋገሪያ ከሆነው ጉዳይ ውስጥ የዲ/ን ዳንኤልና የፕሮፌሰር መስፍን ጉዳይ መሆኑ ይታወቃል ፡፡ ፕሮፌሰሩ በ83 እድሜ ዘመናቸው በኢትዮጵያ ታሪክ ላይ ያዩትንና ያስተዋሉትን  በመጽሀፍ መልክ ለንባብ አብቅተዋል ፡፡ ዲ/ን ዳንኤልም ፕሮፌሰሩ የጻፉት መጽሀፍን በራሱ እይታ ተችቷል ፡፡ ይህ ጽሁፍ መጻፉ ፤ ለሂስ መቅረቡና ሰዎች የራሳቸው አስተያየት መስጠታቸው ተገቢ ቢሆንም ጥቂት አስተያየት ሰጪዎችና ሂስ አቅራቢዎች “ዲያቆን” የሚለውን ማዕረግ ከየት እንደተገኝ ፤ ለዲ/ን ዳንኤል ማን እንደሰጠው ያላስተዋሉ የፕሮፌሰሩን ወይም የዲ/ን ዳንኤልን ሃሳብ ከመሞገት ይልቅ ወደ ሰዎቹ ማዕረግ እና ስብዕና ላይ ያተኮረ አስተያየት ሲሰጡ ተስተውሏል ፡፡ ፕሮፌሰር መስፍንም የፕሮፌሰርነትን መአረግ ከመሬት ወድቆ እንዳላገኙት ሁሉ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንም የዲያቆንነት ማዕረግ ዝም ብሎ አይሰጥም ፡፡ ትንሽ ቢመስል ዋጋ ተከፍሎበታል ፡፡ ቤተክርስቲያን ለአንድ አገልጋይ የምትሰጠውን ማዕረግ አንቋሾ ፤ አውርዶ ፤ እንደማይገባው አድርጎ አስተያየት መስጠት “ባለቤቱን(ማዕረግ ሰጪውን)  ካልናቁ ….” ነው የሚሆነው፡፡ አንድ ሰው ስለ ዲ/ን ዳንኤል በሰጠው አስተያየት ላይ የፈለገው ማለት ይችላል ፤ ማዕረጉን ግን ከፍ ዝቅ ማድረግ ተገቢ ነው ብለን አናምንም ፡፡ ለማንኛውም የዲ/ን ዳንኤል አስተያየትን በአንባቢያ ጥያቄ መሰረት ከላይፍ መጽሄት ላይ በመውሰድ  እንዲህ አቅርበነዋል፡፡
ላይፍ፡- በቅርቡ ሰማያዊ ፓርቲ በብሔራዊ  ቲያትር ፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም ባዘጋጁት ‹‹መክሸፍ እንደ ኢትዮጵያ ታሪክ›› በተሰኝ መጽሀፍ ዙሪያ ውይይት ተደርጎ ነበር፡፡ በውይይቱ ግምገማቸውን ከሚያቀርቡ ሰዎች አንተ አንዱ ስለመሆንህ ተነግሮ ነበር፡፡ ነገር ግን በእለቱ በስፍራው አልተገኝህም፡፡ ምክንያትህ ምንድነው ነበር ?
 ዲ/ን ዳንኤል፡- ይህንን ነገር ካነሳህው እናውራው፡፡ መቼም አንድ ፕሮግራም መጋበዝህ ለሦስተኛ ወገን ከመነገሩ በፊት የአንተ ፈቃደኝነት ይጠየቃል፡፡ ፕሮግራምህ እንዴት ነው? በዚያ ወቅት  ነጻ ነህ ወይ ? አገር ውስጥ ትኖራለህ? ተብሎ ይጠየቃል፡፡ እነዚህ ነገሮች ግን ለእኔ አልተደረጉም፡፡ ስለ ፕሮግራሙ መጀመሪያ ደውሎ የነገረኝ ብርሀኑ ደቦጭ ነበር፡፡ እሱም ያለኝ “በፕሮፌሰሩ መጽሀፍ ዙሪያ ውይይት ተዘጋጅቷል ከቻልክ ሄደን የሚደረገው ነገር እንመለከታለን” ነው ያለን፡፡  ከዚህ ውጪ የተነገረኝ ነገር አልነበረም፡፡ ቀኑ እየተቃረበ ሲመጣ አርብ እለት አንድ ሰው ከአሜሪካ ደውሎ “በውይይቱ ላይ የምታቀርበውን የመጽሐፍ ግምገማ  ቀድተህ ላክልኝ” አለኝ፡፡ እኔ እኮ አልተጋበዝኩም አልኩት ፤ “ኧረ ተው መጋበዝህን ከፌስ ቡክ ላይ አይቼ ነው የደወልኩልህ” አለኝ ፤ እኔም “እስኪ ላከውና እኔም ልየው” አልኩት፡፡ እኔም በፕሮግራሙ ጥናት አቅራቢ መሆኔን ከፌስ ቡክ ላይ ተመለከትኩኝ፡፡ ቅዳሜ ቀን አዲስ አድማስ ጋዜጣ ላይ ስሜ ወጥቶ አየሁትኝ፡፡ የዚያን እለት የፕሮግራም አዘጋጅ ነኝ ያለ ሰው ስልክ ደውሎ ‹‹ነገ ጽሁፍ ታቀርባለህ›› አለኝ፡፡ እኔም “እንዴት ያለ እኔ ፍቃድ ስሜን በጋዜጣ በማውጣት ፈቃደኝነቴን ዝግጁነቴን ባልተጠየኩበት ሁኔታ ፕሮግራም ትይዛላችሁ?” ስለው ብርሀኑ ደቦጭ አልነገረህም እንዴ አለኝ፡፡ ብርሀኑ ከእኔ ውጪ ከሶስተኛ ወገን ከመስማቱ ውጪ መጽሀፉን በመገምገም እንደምናቀርብ የሚያውቀው ነገር እንዳልነበረ መጀመሪያ በደወለልኝ ቀን ከነገረኝ ነገር በመነሳት ከማወቄ ውጪ ብርሀኑ ከዚህ ወዲህ አልደወለልኝም፡፡  ሰማያዊ የሚባል ፓርቲ የዝግጅቱ አዘጋጅ መሆኑን ያወኩት ከዚያ በኋላ ነው፡፡ መቼም አንድ ፓርቲ ሰውን ሲጋብዝ በይፋ የፓርቲው ማህተብ በማስፈር እንዴት ደብዳቤ እንዲደርስ አያደርግም?  ለአንድ ሰው መብት መከበር እታገላለሁ የሚል ፓርቲስ  ያልጋበዘውን ሰው እንዴት እከሌ በፕሮግራሙ ላይ የጥናት ወረቀት ያቀርባል በማለት በጋዜጣ ያስነግራል? ለእኔ ነገሩ በጣም አስገራሚ ሆኖ አልፏል፡፡

Ingen kommentarer:

Legg inn en kommentar